የኖህ መርከብ
From Wikipedia, the free encyclopedia
የኖህ መርከብ ወይም ሐመር (ዕብራይስጥ፦ תיבת נח /ተይባት ኖዋሕ/፤ ዓረብኛ፦ سفينة نوح /ሣፊና ኑህ/) በመጽሐፍ ቅዱስ (ኦሪት ዘፍጥረት ምዕ. 6—9)፣ በቁርዓንም (ሱራ 11 እና 71)፣ እንዲሁም በሌሎች «አብርሐማዊ» የተባሉ ሃይማኖቶች ጽሑፍ ዘንድ፤ ኖህን፣ ቤተሠቡንም፣ ከዓለም እንስሶችም ምሳሌዎች ከማየ አይኅ ለማዳን የተሠራ ታላቅ መርከብ ነበረች።
በዘፍጥረት የተገኘው መሠረታዊ ታሪክ እንደሚለው፣ እግዚአብሔር በሰው ልጅ ክፋት አዝኖ[1] ብልሹውን ዓለም ለማጥፋት ወስኖ ነበር። ሆኖም ኖህ ጻድቅ ሆኖ እራሱን፣ ቤተሠቡንም የመሬት እንስሶችንና አዕዋፍንም የምታድን መርከብ እንዲገነባ አዘዘው። የጥፋት ውኃ ከዚያ ምድሩን አጥፍቶ ውሆቹ መልሰው የብስ እንደገና ታየና መርከቢቱ በአራራት ተራሮች ላይ ዐረፈች። በመጨረሻ እግዚአብሔር ከኖህና ተወላጆቹ ጋራ ቃል ኪዳን ገባ።
ለዚህ መተረክ ብዙ ጊዜ በአብርሃማዊ ሃይማኖቶቹ በኩል ሰፊ ዝርዝሮች ተጨምረዋል። እነዚህ ዝርዝሮች ከሥነ-መለኮታዊ ትርጉሞች ጀምሮ ለተግባራዊ ጉዳዮች የሆኑ መላምታዊ ፍቾች እስከሚነኩ ድረስ ሊሆኑ ይችላሉ። በ19ኛው ክፍለ-ዘመን ላይ፣ በተለይ በምዕራብ ዓለም በብዙዎቹ የሳይንስና የሥነ ጽሑፍ ሊቃውንት አስተያየት፣ መተራረኩ አፈ ታሪክ ብቻ እንጂ በዕውኑ አይሆንም በማለት ተጠራጠሩ። ዳሩ ግን በመጽሐፍ ቅዱስ ትክክለኛነት የሚያምኑት ሰዎች እስካሁን አይነተኛና ዕውነተኛ ታሪክ መሆኑን ቆጥረውታልና እስከዚህ ቀን ድረስ ለመርከቢቱ ማረፊያ ተራራ አንዳንድ ፍለጋ ሲካሄድ ነው።